Latest Ethiopian news: የሰሜን እዝ የጦር ክፍሎች በጥሩ የዝግጁነት አቋም ላይ ይገኛሉ – ሌ/ጄነራል ባጫ ደበሌ

ከሽራሮ እስከ ዛላንበሳ ድረስ ያሉት የሰሜን እዝ የጦር ክፍሎች በአሁኑ ሰዓት በጥሩ የዝግጁነት አቋም ላይ እንደሚገኙ ሌተናል ጀኔራል ባጫ ደበሌ ገለጹ፡፡

ሌተናል ጀኔራል ባጫ ደበሌ በወቅታዊ ጉዳችን አስመልክተው ዛሬ በሰጡት መግለጫ ከሽራሮ እስከ ዛላንበሳ ድረስ ያሉትን የሰሜን እዝ የጦር ክፍሎች በአካል በመገኘት ምልከታ ማድረጋቸውን ገልፀዋል። 

በሰራዊቱ ላይ የተፈፀመው በደል በወገን ላይ የማይፈፀም ድርጊት ከመሆኑም ባለፈ ኢሰብዓዊ መሆኑን ሌተናል ጀኔራሉ ገልጸው፣ ሰራዊቱን ለበለጠ እልህና ቁጭት ያነሳሳው መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ሠራዊቱን ከውስጥ ለማፍረስ የሰሜን ዕዝን የሬዲዮ መገናኛ አዲስ አበባ በሚገኘው የመገናኛ ሀላፊ አማካኝነት ወደነሱ ማዞራቸውን ያነሱት ሌተናል ጀኔራል ባጫ ደበሌ፥ በዚህም መከላከያ እና ጦሩ እርስ በርሱ እንዳይገናኝ አድርገዋል ነው ያሉት፡፡

በዚህም የሠራዊቱን የወር ደመወዝ እና ቀለቡን በመውሰድ አዛዦችን ማፈናቸውንም አንስተዋል፡፡

ሰራዊቱም ይህ ሁሉ ተፈጽሞበት በጀግንነት መዋጋቱንም ነው ያወሱት፡፡

በወቅቱ በተደረገው ውጊያ ከትግራይ ልዩ ሃይል በተጨማሪም በዛላንበሳ፣ በሽራሮ፣ በራማ ፣ በፆረና እና በሌሎች ቦታዎች የኦነግ ሸኔ አባላት ባንዲራቸውን ይዘው አብረው ተዋግተዋልም ነው ያሉት በመግለጫቸው፡፡

(በአስታርቃቸው ወልዴ)

Say Something