«የመከላከያ ሠራዊት ዳንሻን፣ ባከርን እና ከሽራሮ እስከ ሽሬ ያሉ አካባቢዎችን ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥሯል» – ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ

የመከላከያ ሠራዊት ዳንሻን፣ ባከርን እና ከሽራሮ አስከ ሽሬ ያሉ አካባቢዎችን ሙሉ በሙሉ መቆጣጠሩን የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ምክትል ኤታማዦር ሹም እና የኦፕሬሽን ዘርፍ ኃላፊ ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ አስታወቁ። 

ለኢትዮጵያ ነቀርሳ የሆነው ከሀዲው የህውሓት ቡድን ካልተደመሰሰ ሀገር ሰላም እንደማትሆንም ምክትል ጠቅላይ ኢታማዦር ሹሙ ገልፀዋል። 

ጄኔራል ብርሃኑ ጁላ የመከላከያ ሠራዊቱን የግዳጅ እንቅስቃሴ አስመልክተው እንዳስታወቁት፣ የመከላከያ ሠራዊቱ ዳንሻን፣ ባከርን እና ከሽራሮ አስከ ሽሬ ያሉ አካባቢዎች ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥሮ ወደ ፊት እየገሠገሠ ይገኛል።

መከላከያ በከሀዲ ቡድኑ እጅ ያሉ ከባድ መሳሪያዎች ሙሉ በሙሉ ማውደሙን አመልክተው፣ እንደ ተምች በየቦታው ሠራዊቱን የከበበውን ኃይል እያራገፈ መሆኑን ጠቁመዋል። ትናንሽ ክፍሎችን ከቦ የነበረው ኃይልም በሠራዊታችን ታላቅ ጀግንነት ተደምስሰዋል ብለዋል። ከፍ ያለ ቁጥር ያለው የክልሉ ልዩ ኃይልና ሚሊሻ ምርኮኛ እየሆነ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።

መላው የኢትዮጲያ ህዝብ ለሰራዊቱ እያሳየ ያለው ድጋፍ ከፍ ያለ የሞራል ልእልና እንዳላበሰውም አስታውቀዋል። ለኢትዮጵያ ነቀርሳ የሆነው ይህን ከሀዲ ቡድን በመደምሰስ የሕግ የበላይነትና ህገመንግስታዊ  ስርዓት ለማረጋግጥ በብቃት እየተሰራ መሆኑን ኢፕድ ዘግቧል ።

የመከላከያ ኃይሉ ሕዝብ እንዳይጎዳ ለማድረግ ሕዝብ እና ጽንፈኛ ኃይሉን ለይቶ ለመምታት በጥንቃቄ እየተንቀሳቀሰ መሆኑንም ጄኔራል ብርሃኑ ተናግረዋል።

Say Something