የአማራ ክልል ባለሀብት አቶ በላይነህ ክንዴ ለመከላከያ ሠራዊት፣ ለአማራ ልዩ ኃይልና ሚሊሻ 50 ሠንጋዎችን እንዲሁም በጉጂ ዞን ነገሌ ቦረና ነዋሪ የሆኑት አቶ ፍቃዱ ታምሩ 16 ሰንጋዎችን ለሀገር መከላከያ ሰራዊት በስጦታ አበርክተዋል፡፡
በጉጂ ዞን ነገሌ ቦረና ነዋሪ የሆኑት አቶ ፍቃዱ ታምሩ 16 ሰንጋዎችን ለኢፌዴሪ መከላከያ ሚኒስትር ዶ/ር ቀነዓ ያደታ አስረክበዋል። ሰንጋዎቹ 480 ሺህ ብር እንደሚያወጡም ተገልጿል፡፡

የመከላከያ ሚኒስትሩ በርክክቡ ወቅት “ህዝባችን ለሠራዊታችን ያለውን ፍቅር የገለፀበትና የትህነግ ነቀርሳ ቡድን ቶሎ እንዲወገድለት ፍላጎት መኖሩን ያሳያል፤ ሠራዊታችንም በአጭር ጊዜ ውስጥ ቡድኑን ለህግ ያቀርባል” ብለዋል።
ስጦታውን ያበረከቱት አቶ ፍቃዱ ታምሩ በበኩላቸው፣ “ለሠራዊታችን ያለንን አጋርነት ለመግለፅ እኔ ቀደምኩ እንጂ ህዝቡ ከፍተኛ ፍላጎት አለው” ማለታቸውን ከመከላከያ ሚኒስቴር ማሀበራዊ ትስስር ገጽ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
በተመሳሳይ የአቶ በላይነህ ክንዴ ተወካይ አቶ አስማማው አለነ ህይወቱን አስይዞ ህግን ለማስከበር እየታገለ ላለው መከላከያ ሠራዊት፣ ለአማራ ልዩ ኃይልና ሚሊሻ የሚሆን 1 ነጥብ 7 ሚሊየን ብር ወጭ በማድረግ 5ዐ ሰንጋዎችን በመግዛት ለጎንደር ከተማ አስተዳደር ሀብት አፈላላጊ ኮሚቴ ማስረከባቸውን ገልጸዋል፡፡
ሀገርን አደጋ ላይ የጣለው የህወሓትን አሻባሪ ቡድን ለማስወገድ ግንባር ተሠልፎ ህግ በማስከበር ላይ ላለው የሀገር መከላከያና ልዩ ሀይል ከዚህም በላይ ይገባዋል ያሉት አቶ አስማማው፣ ሌሎች ባለሀብቶችም በዚህ ሀገር የማዳን ጥሪ መሣተፍ ይኖርባቸዋል ማለታቸውን ከጎንደር ከተማ አስተዳደር ኮሚዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።