በቦሌ ክፍለ ከተማ ከ2 ሚሊየን በላይ ሀሰተኛ የአሜሪካ ዶላር ተያዘ
በቦሌ ክፍለ ከተማ ከ2 ሚሊየን በላይ ሀሰተኛ የአሜሪካ ዶላር ተያዘ
አዲስ አበባ፣ መስከረም 22፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን በቦሌ ክፍለ ከተማ ከ2 ሚሊየን በላይ ሀሰተኛ የአሜሪካ ዶላር ከእነተጠርጣሪው ይዞ ምርመራ እያደረገ መሆኑን አስታወቀ፡፡
የውጭ ሃገር ዜጋ የሆነው ተጠርጣሪ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 7 ጉርድ ሾላ ሰፈረ ገነት ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በቁጥጥር ስር መዋሉ ነው የተገለጸው፡፡
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጌቱ አርጋው ግለሰቡ ተከራይቶ በሚኖርበት ቤት ውስጥ ሃሰተኛ ዶላር እንደሚያዘጋጅ ጥቆማ መድረሱን ገልጸዋል፡፡
ፖሊስም ጥቆማውን ተከትሎ ባደረገው ክትትል በመኖሪያ ቤቱ ውስጥ ከ2 ሚሊየን 470 ሺህ በላይ የአሜሪካ ዶላር ይዞ እያጣራ መሆኑን ኮሚሽነሩ ገልጸዋል፡፡
በተመሳሳይ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 13 ዛሜሌክስ ሆቴል ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የውጭ ሃገር ዜግነት ያለው ግለሰብ “ከአንድ የአፍሪካ ሃገር ወደ ኢትዮጵያ በዲፕሎማቶች አማካይነት የሚገባ 5 ሚሊየን ዶላር አለ” በማለት ሌላ ግለሰብን በማታለል ገንዘብ ለመውሰድ ሲሞክር የግል ተበዳይ በመጠራጠር ለፖሊስ ጥቆማ መስጠታቸው ተገልጿል፡፡
ፖሊስ ጥቆማውን ተከትሎ ባደረገው ክትትል ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ ሁለት ተጠርጣሪዎችን እና በገንዘብ መጠን የተቆራረጠ ወረቀት በማስረጃነት ይዞ ምርመራ እያደረገ እንደሚገኝ ነው የገለጸው፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከህገ-ወጥ የገንዘብ ምንዛሬ ጋር ተያይዞ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ሰሞኑን ባከናወነው የክትትል እና ቁጥጥር ተግባር 7 ሚሊየን 243 ሺህ 385 የኢትዮጵያ ብር መያዙን አስታውቋል፡፡
ለህገ-ወጥ የገንዘብ ምንዛሬ የተዘጋጁ 117 ሺህ 703 የአሜሪካ ዶላር፣400 ዩሮ፣740 የእንግሊዝ ፓውንድ፣700 የደቡብ አፍሪካ ራንድ፣ 8 ሺህ 50 የተባበሩት ዓረብ ኢሚሬትስ እና ሌሎች የተለያዩ ሃገራት ገንዘቦችን መያዙንም ኮሚሽነሩ አብራርተዋል፡፡
በአጠቃላይ ከህገ-ወጥ የገንዘብ ምንዛሬ እና የብር ኖት ቅያሪ ጋር ተያይዞ ከ15 ሚሊየን በላይ የኢትዮጵያ ብር መያዙን ጨምረው ገልፀዋል፡፡
የመዲናዋን ሰላምና ደህንነት ለማስጠበቅ ዜጎች ከፖሊስ ጋር ያላቸውን ቀና ትብብር አጠናክረው እንዲቀጥሉ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጌቱ አርጋው ጥሪ ማስተላለፋቸውን ከኮሚሽኑ ያገነው መረጃ ያመለክታል፡፡